የጉራጌ ሴቶች በመስቀል
የጉራጌ ሴቶች በመስቀል
የመስቀል በዓል ከአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን
ማለትም ንግሥት እሌኒ ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበትን
መስቀል አስቆፍራ ካስወጣችበት ጊዜ ጀምሮ በእምነቱ
ተከታዮች ዘንድ በድምቀት ይከበራል:: ንግሥቲቷ
መስቀሉ የተቀበረበትን ቦታ ቂራቆስ በተባሉ አባት
ጠቋሚነት ለማግኘት ደመራ አስደምራ ፍለጋ የጀመረችው
መስከረም 17 ቀን እንደሆነ የታሪክ ድርሳናት ያስረዳሉ::
የሃይማኖት አባቶችን አሰባስባ በፀሎት እንዲረዷት
ጠይቃ፣ ከደመራው በሚወጣው ጢስ ጠቋሚነት
መስቀሉ የተቀበረበትን ቦታ አግኝታለች:: መስቀሉም
ከወራት ቁፋሮ በኋላ ወጥቷል:: ከዚያን ወቅት ጀምሮ
መስከረም 16 ቀን የደመራ ሥነ ሥርዓትና መስከረም
17 የመስቀል በዓል ይከበራል::
በንግሥት እሌኒ አማካይነት ከተቀበረበት የወጣው
መስቀል ክፋይ በሰሜን ኢትዮጵያ በግሸን ማርያም
ቤተ ክርስቲያን የሚገኝ ሲሆን፣ በዓሉን ለማክበር ወደ
አካባቢው የሚሄዱ በርካቶች ናቸው::
አዲስ አበባ ውስጥ መስቀል አደባባይ ላይ
ከሚካሄደው ታላቅ የደመራ ሥነ ሥርዓት በተጨማሪ
በየአድባራቱና በየመኖሪያ ቤት ደጃፍም ደመራ
ይደመራል:: ተመሳሳይ አከባባር በሌሎች ከተሞችም
ይከናወናል:: በየአካባቢያቸው በዓሉን የሚያከብሩ ሰዎች
በአደይ አበባ ያሸበረቀ ችቦ ደመራ አብርተው በነጋታው
(በመስቀል በዓል ዕለት) ማለዳ ችቦው የበራበት
ቦታ በመሄድ በአመዱ ግንባር ላይ የመስቀል ቅርፅ
የመሥራት ልማድም አለ::
የመስቀል በዓል ሃይማኖታዊ ይዘት እንዳለ
ሆኖ በየአካባቢው እንደየማኅበረሰቡ ባህልና ወግም
ይከበራል:: ከሌሎች ዐውደ ዓመቶች የመስቀል በዓል
በተለየ በድምቀት በሚከበርባቸው አካባቢዎች የብዙ
ጎብኚዎችን ትኩረትም ይስባል:: በዓሉ በተባበሩት
መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት
(ዩኔስኮ) የማይዳሰሱ ቅርሶች መዝገብ ላይ በዓለም
ቅርስነት የሰፈረውም ለዚሁ ነው::
መስቀል ሲነሳ የጉራጌ ብሔረሰብ ለበዓሉ
የሚሰጠው ልዩ ቦታ ተያይዞ ሊወሳ ይችላል:: የጉራጌ
ዞን ባህል፣ ቱሪዝምና መንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ስለ
በዓሉ አከባበር ባዘጋጀው ጽሑፍ መስቀል፣ ‹‹የመስቀል
በዓል የጉራጌ ብሔረሰብ የበአላት ሁሉ አውራ ሆኖ
ለዘመናት ሲያከብረው የነበረና የሚቀጥልም በዓል
ነው፤›› በማለት ተገልጿል:: ከደመራና መስቀል ቀናት
በፊትና በኋላም በተለያዩ ሥነ ሥርዓቶች የሚከበረው
መስቀል፣ የጉራጌ ተወላጆች ወደቀዬአቸው በመሄድ
በአንድነት የሚያከብሩት በዓል ነው::
የመስቀል በዓል አከባበር ከመስከረም 12 እስከ
ጥቅምት 5 ድረስ በተለያየ ሥነ ሥርዓት የሚቀጥል
ሲሆን፣ ሴቶች ከበዓሉ ዝግጅት ጀምሮ በልዩ ሁኔታ
የሚያከብሯቸው ዕለቶችም አሉ:: መስቀል በጉራጌ
ትልቅ በዓል እንደመሆኑ ዝግጅቱም ሰፊ ነው:: የመስቀል
በዓል ከተከበረበት ዕለት ጀምሮ ለሚመጣው ዓመት
መስቀል መሰናዶ ይጀመራል:: ከትውልድ ቀዬአቸው
ርቀው የሚኖሩ የአካባቢው ተወላጆች ለመስቀል በዓል
ቤተሰቦቻቸውን ለመቀላቀል ውሳኔ ላይ የሚደርሱትም
ከወራት በፊት ነው:: ተወላጆቹ የአቅማቸውን ያህል
ገንዘብ አጠራቅመው ወደ ትውልድ መንደራቸው
ያቀናሉ::
ለመስቀል በዓል ዝግጅት ሲደረግ ሥራ በጾታና
በዕድሜ ይከፋፈላል:: በዚህ መሠረት ልጆችና ወጣት
ወንዶች ለደመራ የሚሆን እርጥብ እንጨት ከጫካ
ለቅመው፣ ከደረቀ በኋላ ይፈልጣሉ:: በዕድሜ ከፍ
ያሉት አባወራዎች ደግሞ ለበዓሉ የሚታረዱ ከብቶችን
ሳር በመቀለብ ያደልባሉ::
ሴቶች በበኩላቸው ለሚመጣው መስቀል በዓል
የሚሆን ቅቤ ማጠራቀም የሚጀምሩት የመስቀል
በዓል እንደተጠናቀቀ ነው:: የወራት ዝግጅታቸው ቤት
ማሳመርንም ያካትታል:: በዓሉ ሦስት ወራት ሲቀሩት
መሰናዶውም ይጧጧፋል:: ወጣት ሴቶች ቤት ቀለም
ሲቀቡ፣ የእማወራዎች ድርሻ እንሰት ፍቆ ማዘጋጀትና
ጅባ መሥራት ይሆናል:: በተለይ የቡሔ በዓል ከተከበረ
በኋላ የመሰናዶውን ፍጥነት ይጨምራሉ::
የጉራጌ ሴቶች የመስቀል በዓል መከበር
በሚጀምርበት መስከረም 12 ቀን ለምግብ ማቅረቢያ
የሚውሉ ቁሳቁሶችን ከግርግዳ ያወርዳሉ:: ዕለቱ
ሌማት ይወርድቦ ቀነ በመባል የሚታወቅ ሲሆን፣
በዕለቱ የመመገቢያ ቁሳቁሶች እንዲሁም ቤት ይፀዳል::
በየቤቱ አዳዲስ ጅባዎች ይነጠፋሉ:: ቀጣዩ ቀን ወሬት
ያሸና ወይም ወልቀነ ይባላል:: ሴቶች የጎመን ክትፎ
የሚያዘጋጁበት ሲሆን፣ ከቆት የሚበላበት ዕለት በመባል
ይታወቃል::
በጉራጌ ባህል መስከረም 14 ደንጌሳት ይባላል::
የጎመን ክትፎ በሸክላ ጣባ ለመላው ቤተሰብ
የሚቀርብበት ዕለት ነው:: በዕለቱ የሚወጣውን ወጪ
በሙላ የሚሸፍኑት ሴቶች ናቸው:: ሴቶች ዓመቱን
በሙሉ ለመስቀል ባጠራቀሙት ገንዘብ ሙሉ ዝግጅቱን
ሸፍነው ቤተሰባቸውን ያስተናግዳሉ:: በደንጌሳት ማታ
በየቤቱ ደመራ ይለኮሳል:: ሥርዓቱ የባዮፕ ኧሳት ቀን
ይባላል:: ደመራው ሲቃጠል ሴቶች እልልታ ያሰማሉ::
ለበዓሉ በሰላም በመድረሳቸውም ፈጣሪን ያመሰግናሉ::
ወከመያ ወይም ጨርቆስ አልያም በሌላ አጠራሩ
የእርድማይ የሚባለው መስከረም 15 ነው:: በዕለቱ
እያንዳንዱ የቤተሰብ አባል ሁለትና ከዚያ በላይ የደለበ
በሬ ያርዳል:: እርዱ ተጠናቆ የከብት ሥጋ ወደ ቤት
እንደገባ ጥሬ ሥጋ በቅቤ ተነክሮ ይበላል:: ቡና በቅቤም
ይጠጣል::
የአካባቢው ማኅበረሰብ በኅብረት ደመራ የሚያበራበት
የባንዳ ኧሳት ወይም የጉርዝ እሳት የሚባለው መስከረም
16 ቀን ይከበራል:: ዕለቱ በየአድባሩ ደመራ የሚበራበትና
ሃይማኖታዊ ሥርዓት የሚከናወንበት ነው:: ትልቁን
ደመራ የማብራት ሥነ ሥርዓት ሲጠናቀቅ በየአካባቢው
መጠነኛ ደመራዎች ይበራሉ:: ደመራው ሥር ይበላል፣
ይጠጣል፣ ይጨፈራል::
ሥነ ሥርዓቱ ተጠናቆ ወደቤት ከተገባ በኋላ በጣባ
ክትፎ ይበላል:: በነጋታው ንቅባር (የከሰል ማይ) የተባለ
ሥርዓት አለ:: ሥርዓቱ በአንድ አካባቢ ያሉ ዕድርተኞች
ደመራ የተቃጠለበት ቦታ ተሰባስበው ቃል የሚገባቡበት
ነው:: በዕለቱ አዳዲስ የዕድር ዳኞች ይሾሙና ካለፈው
ዓመት ዳኞች ጋር የኃላፊነት ርክክብ ይካሄዳል:: አዳዲስ
የዕድር አባላት ምዝገባም ይኖራል::
መስከረም 18 የፊቃቆማይ ይባላል:: ሴቶች
የተለያዩ የስፌት ቁሳቁሶች ለማዘጋጀት የሚውል
ስንደዶ መልቀም የሚጀምሩበት ነው:: የአካባቢውን
ባህላዊ ዜማ እያሰሙ ስንደዶ ይለቅማሉ:: ከመስከረም
17 እስከ መስከረም 23 ያለው የጀወጀ ወይም የጀወቸ
አማች መጠየቂያ ጊዜ ነው::
በአማች መጠየቂያ ወቅት ሴቶች ለእናቶቻቸው
የፀጉር ቅቤ ለአባቶቻቸው ባርኔጣና ጭራ ይገዛሉ::
ባሎቻቸው ደግሞ ሙክት ይሸምታሉ:: ወቅቱ ልጆች
በወላጆቻቸው እንዲሁም ባለትዳሮች በአማቾቻቸው
የሚመረቁበትም ነው::
የመስቀል በዓል አከባበርን ከሚያጎሉ ሥርዓቶች
መካከል የአዳብና ባህላዊ ጭፈራ ሥነ ሥርዓት ተጠቃሽ
ነው:: አዳብና ከመስከረም 16 ቀን እስከ ጥቅምት
በዓል ባሉት ቀናት ይከናወናል:: በመገበያያ ቦታዎችና
ሌሎችም የጋራ መሰብሰቢያ ቦታዎች አዳበና ሲጨፈር
ወንዶችና ሴቶች ሎሚ፣ ብርቱካንና ሸንኮራ አገዳ
በመለዋወጥ ይተጫጫሉ::
ወጣቶች ክብ እየሠሩ በሚዘፍኑበትና
በሚጨፍሩበት የአዳብና ሥርዓት ብዙዎች የትዳር
አጋራቸውን ይመርጡበታል:: አንድ ወንድ ለወደዳት
ሴት ሎሚ በመስጠት ፍላጎቱን ያሳውቃል:: የወንዱ
ጓደኞች ስለልጅቷ ማንነት አጥንተው ለቤተሰቦቹ
ያሳውቃሉ:: ከዛም ለሴቷ ቤተሰቦች ሽማግሌ በመላክ
የጋብቻ ሒደቱ ይቀጥላል::
ባጠቃላይ በበዓሉ ዝግጅትና አከባበርም ሴቶች
ያላቸውን ጉልህ ሚና ማየት ይቻላል:: የበዓሉ
ማኅበረሰባዊ፣ ባህላዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳም ቀላል
አይደለም:: መስቀል በጉራጌ ብሔረሰብ ዓመቱን
ሙሉ ተለያይተው የኖሩ ቤተሰቦችና አብሮ አደጎች
የሚገናኙበት ነው:: በዓሉ የተጣሉ የሚታረቁበትና
ወጣቶች የሚተጫጩበትም ነው::
መስቀል እንደ ዕድር ያሉና ማኅበረሰቡን
የሚያስተሳስሩ መስተጋብሮች የሚጠናከሩበት ወቅት
ነው:: የጉራጌ ዞን ባህል፣ ቱሪዝምና መንግሥት
ኮሙዩኒኬሽን ስለ በዓሉ አከባበር በድረ ገጹ ያሰፈረው
መግለጫ፣ በዓሉ የቀዬው ሰው የሚመራረቅበትና
ስለቀጣይ ማኅበራዊ ጉዳዮች ዕቅድ የሚወጣበት ነው
ይላል:: በዓሉ በአዲስ ዓመት የሚሠሩ ሥራዎች
እንዴት መከናወን እንዳለባቸው የሚታቀድበት
መሆኑንም ይጠቀሳል::
በመስቀል ስለ ግብርናና ንግድ ሥራ ይወራል::
ወጣቶች ከዕድሜ ባለፀጎች ኃላፊነት ይረከባሉ:: በቢሮው
በተዘጋጀው መግለጫ፣ ‹‹መስቀል ወላጆች ለበዓሉ
የተዘጋጀውን ከብት ከፊታቸው አቁመው ሻኛውንና
ጀርባውን በመዳሰስ ትውልዱን የሚመርቁበት ነው::
ለአገር ሰላምና ብልፅግና ፈጣሪን የሚለምኑበት፣
የተቸገረ የሚጠየቅበት፣ በዳይና ተበዳይ ይቅር
የሚባባሉትም ወቅት ነው፤›› በማለት ተገልጿል::
ምንጭ፡- ሪፖርተር ቅፅ 22 ቁጥር 17 13